Monday, December 24, 2012

የዝምታ ጩኽት…..!



                              የዝምታ ጩኽት…..!

       ከቀኑ 6፤00አካባቢ ተንቀሳቃሽ ስልኬ አቃጨለች፡፡ ጥቅምት 1/2005ዓም እነሆ ዛሬ የምናወራላት የትዕግስት አለምነህ ድምጽ ነው፡፡ ብዙ አወራን የትውውቃችን ሰበብ ይሄው የእሌክትሮኒክስ መረጃ መረብ (ፌስ ቡክ) ነው ፡፡እንደዋዛ በዚሁ መረጃ መረብ ከረጅም ጊዜ ጀምሮ ስሜቴን ሲነካኝ የምጽፋቸውን የግጥም ሙከራዎቼን በማድነቅ በማበረታታት በወዳጅነት በመጣመር ከሰነበትን በርካታ ወዳጆቼ መሃል አንዷ ሆና ተገኝታለች፡፡

በስልክ ቆይታችን አንድ የሚያስደንቅ የብስራት ዜና ነገረቺኝ…….፡፡ የበኩር ልጇ የሆነውን የግጥም መድብሏን ለማስመረቅ ዋዜማ ላይ ነች…..!፡፡ ቀጠለች በደስታዋ ቀንም እንድገኝና ከውስን ገጣሚያን መሃል እኔም የግጥም ስራዎቼን እንዳቀርብ መጽሃፏን እንድመርቅላት ጋበዘቺኝ ፡፡ ሌላ ደስታ…….!!፡፡እንኳንስ ለትልቅ ደረጃ፤ለአቅመ ምርቃት ለበቃ የግጥም መድብል ቀርቶ ሁለት ስንኝ ጽፎ ለሚያስነብበኝ ትልቅ ቦታ ሰጣለሁና የገጣሚ ትግስት አለምነህን ግበዣ በደስታ ተቀበልኩት፡፡



      ከገጣሚዋ ጋር በስልክ ከተገናኘን ከአንድ ሳምንት በኋላ በናፍቆትና በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የዝምታ ጩኅት የግጥም መድብል በይፋ የሚመረቅበት ቀን ደረሰ፡፡ጥቅምት 8/2005ዓም ቦታው አዲስ አበባ የሚገኘው የኢትዮጲያ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጽሀፍት ኤጀንሲ የቀድሞ ስሙ ወመዘክር በአዲሱ ህንጻ ትንሿ አዳራሽ እንደሚሆን ቀደም ብሎ ተነግሮኛል፡፡እናም ለዝግጅቱ ከአዲስ አበባ በምስራቅ አቅጣጫ 100 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ላይ ከምትገኘው ናዝሬት (አዳማ) ከተማ ቀጥር ላይ በመነሳት ጉዞዬን ጀመርኩ፡፡

    ከሁለት ሰዓት የጉዞ ቆይታ በኋላ አዱ ገነት ስደርስ ከሰዓት በኋላ 9ሰዓት አካባቢ ሆኗል፡፡ ጊዜ የለም በቀጥታ ወደ ድግሱ ስፍራ አቀናሁ 10 ሰዓት አካባቢ የምረቃት ስነ ስርዓቱ ይጀምራል ፡፡ ከዛ በፊት ግን በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ ለሚቀርቡ ግጥሞች ለመነጋገር የተመረጡ ገጣሚያን ቀድመው እንዲገኙ በተነገረን መሰረት ቦታው ላይ ደርሻለሁ፡፡

ከዚህ በፊት የማውቀው የቀድሞው ወመዘክር ህንጻ ከበስተጀርባው ግዙፍ ዘመናዊ ህንጻ ተገንብቶ መጠርያውም ተቀይሮ ጠበቀኝ፡፡ ለደቂቃዎች በትዝታ ወደኋላ መጓዜን አልደብቅም…..! ከረጅም አመት በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ ወቅት አልፎ አልፎ እገለገልበት ነበር እነሆ ዛሬ በልዩ አጋጣሚ በድጋሚ ለማየት በቃሁ…እንዴት ደስ ይላል……..!!!፡፡ በተለመደው ሁኔታ ዋናው በር ላይ የፍተሻ ስነ ስርአቱን አጠናቅቄ በጥበቃ ሰራተኞቹ ጠቋሚነት ወደ ትንሿ አዳራሽ ለመሄድ የትልቁን ህንጻ ደረጃ ወጥቼ እንደጨረስኩ በስተግራ ካለው በረንዳ ላይ ደጋሽዋን ገጣሚ ትግስት አለምነህን ለዓይነ ስጋ ለመጀመርያ ጊዜ ለመተያየት በቃሁ፡፡ ክብ ፊቷ ላይ የደስታ ብርሃን ተረጭቷል…..! አጠር ያለች ድንቡሽቡሽ ገጣሚ…..፡፡ በዚህ መልኩ አልጠበኳትም ግምቴ መስመሩን ስቷል.. እሷ ግን ቀድማ አውቃኝ ኖሮ እንደ ጸሃይ በሚያበራ ፈገግታዋ ተቀበለችኝ “እንኳን ደስ አለሽ” አልኳት ለፈገግታዋ መልስ ፡፡ ከገጣሚዋ ጋር አንድ ሰው ቆሟል …በቁመት አጭር ቀጭን ጸጉሩ ትንሽ ገባ ያለ ፍጥጥ ያሉና ንቁ የንስር አይን ያሉት …….! አላውቀውም ትኩር ብሎ ይመለከተኝ ነበር፡፡ በዝግጅቱ ላይ ተጋባዥ ሆኖ አንድ ግጥሙን ካቀረበልን በኋላ ግን ሰውየውን የማወቅ ጉጉቴ ጨመረ ……እናም ተዋወቅን ፡፡ ጋዜጠኛ እና ደራሲ ወሰን ሰገድ ገብረኪዳን ይባላል ፓ ፓ ፓ “ህዝብ ማለት” የሚል ርዕስ ያላትን ግጥሙን አንብቦል ወድጃታለሁ እራሴንም ቆም ብዬ እንድመለከት፤እንዳስብ ረድቶኛል “የቃሊቲ ሚስጥሮች” የሚል በእውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን መጽሀፍ እንዳለው ሲነግረኝ ማመን አቃተኝ ፡፡ መጽሃፉን ለማንበብ አንድ ቀንና አንድ ለሊት ብቻ ነው የፈጀብኝ…..! አንድ ጊዜ ማንበብ ከጀመሩ ለማቆም ይከብዳል ልብ አንጠልጣይ እና በአንድ ወቅት በህይወት አጋጣሚው በእስር ቤት ስለደረሰበት ስላየው ሁኔታ ይተርካል….፡፡

                                                                               ©   ©   ©

                                     ሰዓት እየሄደ ነው የተጠበቁ ገጣሚያን አልመጡም አዳራሹም ጭር ብሏል የመጽሃፍ ምርቃት መሆኑን የሚነግረኝ አንዳችም አሻራ አጣሁ……“እንዴት ነው ነገሩ” አልኩኝ በልቤ….. “መቼም ይሄ የሃበሻ ቀጠሮ የሚባለው መጥፎ አመል እንደተጣባን እስከመቼ ይቀጥላል……?”ብቻዬን አወራሁ ፡፡ ተመልሼ ወደ በረንዳው ወጣሁ ገጣሚዋ በተንቀሳቃሽ ስልኳ እዚም እዛም ትደውላልች ቅድም በፈገግታ የተሞላው ፊቷ ጉም የሸፈነው ሰማይ መስሏል……አሁንም ከስልኳ ጋር ጆሮዋን እንዳጣበቀች ነው፡፡  ልረብሻት አልፈለኩም “ተመልሼ እመጣለሁ” በሚል በእጅ ምልክት አሳይቻት ደረጃውን ወረድኩ…..፡፡የቀድሞውን ወመዘክር ዙርያ ገባውን በትዝታ መነጥር መቃኘት ጀመርኩ…….አዲሱ ህንጻ በጣም ያምራል ወደ ውስጥ ዘልቄ ለማየት ባልታደልም እጅግ በጣም ዘመናዊ የሆነ በርካታ አገልግሎትም እንዲሰጥ ተደርጎ የተሰራ መሆኑን ለመገመት አያዳግትም፡፡ በህንጻው መውጫ በረንዳ ላይም እንዲህ የሚል ጽሁፍ በእምነበረድ ላይ ተጽፎ አነበብኩ፡፡ “ የብሄራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጽሃፍት ኤጀንሲ ዘርፍን በዘመናዊ መልክ በማደራጀት ጥናትና ምርምር እንዲስፋፋእና የመረጃ ሃብቶች ተጠብቀው ለትውልድ እንዲተላለፉ ለማድረግ የኤፌድሪ መንግስት በሰጠው ልዩ ትኩረት መሰረት ይህ ህንጻ ተገንብቶ በክቡር አንባሳደር ተሾመ ቶጋ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ሰኔ 28/2000 ዓም በክብር ተመረቀ ” ይላል፡፡ ከፍተኛ ትኩረት እንደተሰጠውና በኤጀንሲ ደረጃ መቋቋሙ ገዢውን መንግስት ሳላመሰግን አላልፍም፡፡በዚሁ መልኩም በርካታ መጽሃፍት ቤቶች በርካታ ሙዚየሞች ቢከፈቱ ፍላጎቴም ምኞቴም ነው እንዲህ የምንጮህለት “ የሚያነብ ትውልድ…. ! ” የምንፈጥረው የተመቻቸ የማንበቢያ ቦታና ምቹ ሁኔታ ስንፈጥርለት ነው ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለኛው ልማታዊ ባለሃብቶች ከሰማይ ጠቀስ ዘመናዊ ህንጻዎቻቸው ቢያንስ አንዱን ክፍል ለቤተ መጽሃፍት ቢያውሉት መጽሃፍትን በመግዛት እንዲሁም ከለጋሽ ድርጅቶች ጋር በመተባበር፤በመሰብሰብ የንባብ ባህልን ለማሳደግ ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ ለመጠቆም እና በመማጸንም ጭምር እጠይቃለሁ ፡፡

                                                                          ©     ©    ©

                አሁን ተንቀሳቃሽ ስልኬ አቃጨለች ከገጣሚዋ የመጣ መልእክት ነው፡፡ተመልሼ ወደ ትንሿ አዳራሽ ገባሁ…….፡፡ቅድም ባዶ የነበረው አዳራሽ የተወሰኑ ገጣሚያን ተሰባስበው ጠበቁኝ ፡፡ ሁሉንም ማለት ይቻላል ለዐይነ ስጋ ለመጀመርያ ጊዜ መተያየታችን ነው፡፡ በዚሁ በማህበራዊ መረጃ ድህረ ገጽ (ፌስ ቡክ) በሚለጥፉት ወይም በሚያስተላልፉት የግጥም ስራዎቻቸው እንተዋወቃለን፡፡ ወደፊት ተስፋ የሚጣልባቸው ገጣሚያን መሆናቸውን መመስከር እፈልጋለሁ፡፡ ወቅታዊ የሆኑ የተለያየ ማህበራዊ ህይወትን የሚዳስሱ በቀላል ቋንቋ እና በምስል በተደገፈ የግጥም መልእክቶቻቸው እያዝናኑ ቁም ነገር የሚያስጨብጡ ናቸው…..፡፡ከዛ ባሻገር በዚሁ የመረጃ መረብ ስለሚለቀቁ የስነ ግጥም ስራዎች ጠንካራና ደካማ ጎን የግጥም አንባቢያንን ከመሳብ አኳያ እያደረጉት ያለውን አስተዋጽኦ ጠለቅ ያለ ሙያዊ አስተያየት ለመስጠት ጊዜ ወስዶ በስነ ጽሁፍ እና ስነ ግጥም በሳል እውቀት ያላቸው ባለሙያዎች ሃላፊነት ወስደው የበኩላቸውን እንዲወጡ መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡

           ጀንበት ማዘቅዘቅ ጀምራለች …..የቀን ውሎዋን አጠናቃ ጠልቃ ከመሰወሯ በፊት ግን አርፍደው የመጡ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች የምስልና የመቅረዘ ድምጽ መሳሪያዎቻቸውን በማስተካከል ተጠምደዋል ቅድም ባዶ የነበረው የመድረኩ ቀኝ ግድግዳ ጥግ የምረቃ የግጥም መጽሃፏን የፊት ሽፋን ምስል እና የምርቃቱን ብስራት የሚያመላክት ሸራ ተወጠረ፡፡ እየተንጠባጠቡ በሚመጡ የበዓሉ እድምተኞች ትንሿ አዳራሽ እየሞላች ነው ……!፡፡ አሁን በግጥም ደራሲዋ አማካኝነት ለግጥም አቅራቢዎች “የዝምታ ጩኅት” ተከፋፈለች….፡፡ እጄ የገባችው የግጥም መድብል የፊት ሽፋን ስዕል እጅግ በጣም ማርኮኛል፡፡አንዲት ውብ ኮረዳ ሴት በርካታ የቢራቢሮ ነፍሳት ወደ እሷ ሲተሙ ያሳያል…..፡፡ እንደሚታወቀው ቢራቢሮዎች  ለዓይን ከሚማርኩ አበቦች ጋር ልዩ ቁርኝት አላቸው ምግባቸውንም የሚያገኙት የመኖር ሕልውናቸው የተመሰረተው በአበቦች ላይ ይመስለኛል እኛ በማይገባን ለነሱ በሚጣፍጥ የማር ወለላ ከአበቦች ላይ ይቀስማሉ፡፡ እግረ መንገዳቸውንም የአበቦችን ዘር የማብዛት ስራ ይሰራሉ….፡፡ በምስሉ ላይ የምንመለከታት ውብ ሴት እንደ ቆንጆ አበባ እንውሰድና ቢራቢሮዎቹ ወደ ተምሳሌቷ ቆንጆ ይተማሉ፡፡ እንድም እንደ ስዕሉ ገለጻ በልጅቷ ውበት ተስበው በርካታ ወንዶች እየተከተሏት ነው…፡፡እሷ ደግሞ ለከጀላት ወንድ ሁሉ መሆን አትችልም አንዱን መምረጥ ይኖርባታል፡፡ በመሆኑም በቀላሉ ለሷ የሚሆንን ወንድ ለመለየት ይቸግራት ይሆናል፡፡ስለዚህ ከራሷ ጋር የምታደርገውን ሙግት፤ግጭት፤ፍጭት የነገሩን ከባድነት በቀላሉ በዓይነ ህሊናችን እንዲመጣ ያደርገናል ፡፡እንግዲህ እንደኔ  መገለጥ ፤መረዳት ወይም የማወቅ አቅም በወፍ በረር የታዘብኩት ይሄንን ነው፡፡ለግጥም መድብሏ የተሰጣት ርዕስና የሽፋን ስዕሉ አልገጠመልኝም ፡፡እስቲ ለግጥም መድብሏ የተሰጣት የርዕስ ግጥም ጭብጥ አንብበን እንመለስ፡፡

የዝምታ ጩኅት

እንዲያ ስለፈልፍ ከቁብ ያልቆጠረኝ

ተው ስል ስማጸነው ዞሮ እንኳን ያላየኝ

ተስፋዬን ቆርጨ ብሄድ ሳላወራው

በዝምታዬ ውስጥ ጩኅቴ ተሰማው፡፡

ያንተኑ ጨለማ ብትሰጠኝ ወርሼ

ከዝምታህ ጠበል ጠዲቅ ተቋድሼ

ዝም አልኩ ለፋሁ

ተከትዬ ጠፋሁ

የግርግሜ ኩራዝ ጭላንጭሏ ደክሞ

ብቸኛው ብቻዬ ብቻ ሲሄድ ከርሞ

ሰላሜን ካከኘሁ ከብቻህ ጋር ቆሞ

የቀረው ዘመኔን ልኑር በአርምሞ፡፡

• • •

    

                                                                    ©        ©        ©

             የምርቃት ዝግጅቱ ሊጀመር የተወሰኑ ደቂቃዎች ቀርተውታል፡፡የእለቱ የክብር እንግዳ የሆነው ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ ጥቁር ቦርሳውን በትከሻው እንዳንጠለጠለ በፈገግታ ጠሞልቶ ወደ አዳራሹ ገባ፡፡ ረጅም ነው…. ሙሉ ወንዳ ወንድ ሰውነት የታደለ……እራሱ ላይ አንድም ጸጉር የለውም ግን ያምራል ሁላችንም በክብር ተቀበልነው…፡፡በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስነ ጽሁፍ መምህር የሆነው ዶ/ር በድሉ ከዚህ በፊት ቤይሩት ላይ አስሪዎቿ የሞት አደጋ የደረሰባት የአለም ደቻሳን ልጆች ለመርዳት ዋቢ ሸበሌ ሆቴል በደጉ ኢትዮጲያዊ አባላት በተዘጋጀ የስነ ጽሁፍ ምሽት ላይ ተጋባዥ ሆኜ አንድ መድረክ ላይ የግጥም ስራዎቻችንን ለማቅረብ እና ለመተያየት በቅተናል ፡፡ እነሆ ዛሬ በቅርብ እርቀት በወንበር ተለያይተን ጎን ለጎን ተቀምጠናል….፡፡ ዶ/ር በድሉ ገጣሚ ነው “ሃገር ማለት የኔ ልጅ” የሚል የግጥም መድብል አለው፡፡ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለያዩ መድረኮች በጋዜጣና መጽሄቶች በኪነ ጥበብ ዙርያ ላይ እየሰጠ ያለው ሙያዊ ማብራርያ እና ጥናታዊ ጽሁፎቹ ታዋቂ እየሆነና በተለይ በስነ ጽሁፍ ዙርያ ላይ ለተሰማሩ ጀማሪ እና  ነባር ልምድ ያላቸው ጸሃፍት በሞራል ፤በሚያቀርቡት ጽሁፎች፤ግጥሞች የአርትኦት ድጋፍ  እየሰጠ ያለው አገልግሎት እንደ ዜጋ፤እንደ ባለሙያ እየተወጣ ያለውን ሃላፊነት ማድነቅ፤ማበረታታት እንዲሁም ተገቢውን እውቅና መስጠት “እውቀትህ ይብዛ ለሁሉ ትረፍ ” ብሎ መመረቅ ተገቢ ነው ፡፡ ይሄ ነገር ወጪ የለውም……. ትርፉ ግን ለሙሁሩ የተስፋ ስንቅ አስቋጥሮ በሞራል በጀመረው ተግባር እንዲቀጥል ይረዳዋል ፡፡

እንደዚህ አይነት አጋጣሚ ሊያመልጠኝ እንደማይገባ ውስጤን አሳመንኩት…፡፡ እናም እጄን እየዘረጋሁ

“ጤና ይስጥልኝ ዶ/ር”  አልኩት

“አብሮ ይስጥንኝ ” አለኝ አጸፋውን እጁን እየዘረጋ፡፡ እጅግ እንደማከብረው እንደማደንቀው አንድ የግጥም ስራውን እንዳነበብኩለት ነገርኩት፡፡ ከአንገቱ ዝቅ በማለት ምስጋናውን ገለጸልኝ፡፡ቀጠለናም፤…“አንተ ግን ከየት ነው የመጣኅው? የዚህ ከተማ ልጅ አልመሰልከኝም ” አለኝ ፡፡ መልሴን እየጓጓ ሙሉ ጆሮውን እየሰጠኝ…… ለጥቂት ጊዜም ቢሆን ከኔ ጋር ለማውራት ፈላጎት ማሳየቱ በድፍረት ላወራው አነሳሳኝ፡፡እኔም ግምቱ ትክክል እንደሆነ ለግጥም ምርቃት ከአዳማ(ናዝሬት) እንደመጣሁ በዝግጅቱ ላይም የግጥም ስራዎቼን እንደማቀርብ አጫወትኩት ፡፡ አሁን ሙሉ ለሙሉ ፊቱን ወደኔ አዞረ……….

“ስነ ግጥም ትጽፋለህ?” አለኝ፡፡

“አዎ እሞክራለሁ ቆይ እንደውም….” አልኩትና ለታዳሚው ለማቀብ ከያዝኳቸው አምስት ያህል አጫጭር የግጥም ስራዎቼን አቀበልኩት ፡፡የልቤ ምት ፍጥነቱን ጨምሯል…..! የሆነ የማላውቀው ዝብቅርቅ ያለ ስሜት እየተሰማኝ ነው፡፡የውስጤ ፍርሃት ግን ድብልቅልቅ ካለው ስሜቴ ገዝፎ ፊቴ ላይ ያሳብቃል…..፡፡ ከረጅም ዓመት ጀምሮ በል  ሲለኝ ስሜቴን ሲነካኝ የምተነፍሰው ግጥም በመጻፍ ነው፡፡በተለያየ ጊዜ በተለያየ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ የጻፍኳቸውን ግጥሞቼን ከአስራ ሶስት ዓመት በፊት በአዲስ አበባ የትምህርትና የስራ ቆይታዬ ወቅት ፒያሳ በሚገኘው የሩሲያ ሳይንስና ባህል አዳራሽ(ፑሽኪን አዳራሽ) ወርሃዊ የኪነ ጥበብ ምሽት ይካሄድ ነበር፡፡ እኔም በዛ ዝግጅት ላይ ለሁለት ዓመት በላይ ተካፍያለሁ በዝግጅቱ ላይ ከሚቀርቡ የተለያዩ የኪነጥበብ ስራዎች አንዱ  በተለያዩ የእድሜ ደረጃ ከጀማሪ እስከ ነባር ገጣሚያን የሚቀርቡ ስራዎች ናቸው፡፡በመሆኑም ማንኛውም ገጣሚያን ይመጥናል ብሎ የጻፈውን ግጥሞች ለማእከሉ ያቀርባል ፡፡የቀረቡት ጽሁፎች በዘርፉ ሙያ ባላቸው ገምጋሚዎች ታይተው ቅድመ ግምገማውን ያለፉ ግጥሞች በማስታወቅያ ሰሌዳ ላይ ይለጠፋሉ በቀጣይም ምሽቱ ከመካሄዱ አንድ ሳምንት ወይም ከዛ በፊት ቀድመ ምርመራውን ያለፉ ግጥምና ገጣሚያን እርስ በእርስ የሚገማገሙበት በሙያው ላይ ሰፊ ልምድ ያላቸው ሂስ የሚሰጡበት ….አስተያየት የተሰጡባቸው ግጥሞች ገጣሚያን ያለምንም ማመንታት ለማስተካከልና ለመማማር ፈቃደኛ የሚሆኑበት መድረክ ይዘጋጃል፡፡ገጣሚያን ከምሽቱ ቀን የበለጠ በጉጉት የሚጠብቁት ልባቸው በተከፋፈለ ስሜት የሚሞላበት ……..ለቀጣይ የስነ ጽሁፍ ህይወታቸው አቅጣጫን የሚለዩበት ወሳኝ ቀን በመሆኑ ገጣሚያን እንዲሁም እኔ ምን ጊዜም ሳስታውሰው እኖራለሁ……፡፡ የእህል ውሃ ነገር ሆኖ አዱ ገነትን ብሎም እንዲህ አይነት የኪነ ጥበብ ምሽቶች ፤ የስነ ጽሁፍ ባለሙያዎችን ርቄ በመቆየቴ ባገኘሁት አጋጣሚዎች መጽሃፍ ከማንበብ ግጥሞችን ጽፎ በአቅራቢያዬ ለሚገኙ ወዳጆቼ ከማሳየት በዘለለ የግጥም ስራዎቼን በሳጥን ቆልፌ ለረጅም ዓመታት ከቆየሁ በኋላ ዛሬ በልዩ አጋጣሚ በዘርፉ ከፍተኛ ትምህርትና ልምድ ባካበተው ከዶ/ር በድሉ እጅ ያውም በጣት የሚቆጠሩ ስራዎቼ እና ባለሙያው ፊት ለፊት ተፋጠው ቆመዋል ……….!፡፡ ይሄ ነው የፍርሃቴ ምንጭ ይሄ ነው ያለፈ የፑሽኪን አዳራሽ ጣፋጭ ትዝታዎቼን ያስታወሰኝ……..፡፡ በዚህ አጋጣሚ በወቅቱ የቀንዲል ቤተ ተውኔት መስራች ፤የሩሲያ ሳይንስና ባህል ማዕከል ሃላፊ የነበሩትን ገጣሚና ጸሃፈ ተውኔት አያልነህ ሙላት እንዲሁም ዝግጅቱ እንዲቃና ያለምንም ክፍያ በፍላጎት ሲሰራ የነበረውን መምህር ጌታቸው (ጌቾ) ሳላመሰግን ማለፍ አልፈልግም ፡፡ ጀማሪ ገጣሚያንን ፤የፊልም ባለሙያዎች፤የመድረክ ሰዎች፤ደራሲዎች ለመደገፍ ለማበረታታት ያደርግ የነበረው ጥረት የሚደነቅ ነበር ብዙዎቹ በወቅወቱ የነበሩ ልጆች ለትልቅ  ቁም ነገር ደርሰዋል……! ( በዚህ አጋጣሚ በዚህ ዙርያ ጣፋጭ የፑሽኪን አዳራሽ ትዝታዎቼን ዛሬ ላይ ለስኬት ስለበቁ ወዳጆቼ አንስቼ ለመጻፍ  እሞክራለሁ) የዛ ሰው ይበለን ፡፡

                                                                            ©    ©    ©

        ዝግጅቱ አልተጀመረም ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ አምስቱንም የግጥም ስራዎቼን አንድ በአንድ ካነበበ በኋላ ቀና ብሎ አየኝ…….. ተመልሶ ግጥሞቹን በሁለት ቦታ ለይቶ ያዛቸው ፡፡ የሚሰጠኝን አስተያየት በጉጉትና በጸጋ ለመቀበል ተዘጋጅቻለሁ ፡፡ ሶስቱን ግጥሞቼን ወደኔ በማስጠጋት  “እነዚህን ግጥሞች ወድጃቸዋለሁ ደስ የሚል ጭብጥ የሃሳብ አወራረድ፤ አሰካካቸው ሁሉ ቆንጆ ነው ፡፡ በተለይ ይህችን ግጥም በጣም ነው የወደድኳት ” አለኝና ነጥሎ አንዷን የግጥም ጽሁፍ አሳየኝ ፡፡ይህች ለብቻ ነጥሎ ያሳየኝ የግጥም ርዕስ “ያኔ ነው ፋሲካ ” የምትል ነች ፡፡ይህችን ግጥም ማስታወሻነቷ ስለሃገራችን ማህበራዊ ህይወት ፤ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ወቅታዊዊን የፖለቲካ አካሄድ ወዘተ በደፋር ብዕሩ ጽፎ ለሚያስነብበን ጋዜጠኛና የአንድ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ለነበረው ወዳጄ ነው ያደረኩት በጋዜጠኝነት ህይወቱ ብዙ መንገላታት ብዙ ዋጋ እየከፈለ ነው ……..!አሁንም ለመክፈል ወደኋላ አይልም፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ታሪኩን ሳጫውተው ጋዜጠኛውን ያውቀዋል ማወቅ ብቻም ሳይሆን አሁን አንድ መጽሄት ላይ አብረው ይሰራሉ ፡፡እናም የግጥሟ መልዕክት በትክክል ግቡን እንደመታ መሰከረልኝ ፡፡ ደስታዬ ወደር አልነበረውም “ በቃ አንተም ለማሳታወሻ ውሰዳት ”አልኩት በደስታ ተቀብሎ እግሩ ስር ከወሸቃት ጥቁሩ ቦርሳ ውስጥ ከተታት፡፡ እስቲ ግጥሟን አንብበን እንመለስ፡፡

ያኔ ነው ፋሲካ

ከንፈር የመጠጡ ያዘኑልኝ ሰዎች፤

ጽናቴን ብጠለል ባለሁበት ስከች፤

እብድ ነው እያሉ የለጠፉት ታርጋ፤

እውነት ስትወለድ የኛ ቀን ሲነጋ፤

ያኔ ነው ትንሳኤ ያኔ ነው ፋሲካ፤

ለታመኑት ታምነው የተሰዉ ለታ፡፡

• • •

        በግራ እጁ ለይቶ የያዛቸውን ሁለቱ ግጥሞቼን ማሰተካከል እንዳለብኝ ለግጥሞቹ የሰጠሁት ርዕስና ከግጥሞቹ ሃሳብ ጋር ምንም እንደማይገናኙ በተለይ የቃላት ምጣኔ ፤ዘይቤ አጠቃቀም፤ዜማ የሚሰብሩ አላሰፈላጊ ቃላት እንደተጠቀምኩ ደግሜ ደጋግሜ እንዳየው …የተለያዩ ደራሲያን ገጣሚያንን መድብሎች እንዳነብ በዛች በተጣበበች ደቂቃ ውስጥ በሙሉ ፍላጎት ሲያርመኝ ያሳየው ቀናነት ይበልጥ እንድወደው አደረገኝ፡፡ ምስጋናዬን ቃላት ብቻ የሚገልጸው አይመስለኝም ፡፡በፈለኩት ሰዓት በኪነ ጥበብ ዙርያ መነጋገር እንደምንችል ሙሉ ፈቃደኛ መሆኑን ደውዬ ማግኘት እንድችል የተንቀሳቃሽ ስልክ ቁጥሩን አቀበለኝ፡፡

የባንክ ባለሙያና ገጣሚ ትግስት አለምነህ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ከ1994 ዓም ጀምሮ በቁጥረ 67 የሆኑ የግጥም ስራዎቿን “በዝምታ ጩኅት” ቋጥራ ለህትመት ከማብቃቷ በፊት ለዶ/ር ብሉ ማስገምገሟ በግጥም መድብሉ ዙርያ እያንዳንዱን ሙያዊ አስተያየት መቀበሏ ትክክለኛ እርምጃ ወስዳለች እላለሁ፡፡ ስለዚህም  በዚህ መድብል ውስጥ ስለተካተቱት የግጥም ስራዎች ቴክኒካል ጉዳዮችን አንስቶ ለመተቸት የዚህ ጽሁፍ አቅራቢ ድፍረቱ የለውም ይልቅስ በግጥሞቹ ጭብጥ ዙርያ ሊያስተላልፉ ስለሚፈልጉት መልእክቶች ግጥሞቹን ሲያነብ ስለተመቸውና ስሜቱን ስለነካው ጉዳዮች በቁንጽል እውቀቱ በመዳሰስ ቀሪውን ለአንባቢያን ለመተው ይመርጣል ፡፡ ከዛ በፊት ግን ማምሻውን እጥር ምጥን ብሎ በስኬት ስለተጠናቀቀው የምረቃት ስነስርዓት ፤ በስነ ስርዓቱ ላይ ስላጋጠሙት አስደሳች ገጠመኞች መቋጫ አበጅተን በሙሉ ሃይል ስለ ግጥም መጽሃፏ እንጫወታለን፡፡

                                                                     ©    ©    ©

        ደራሲ ፤ገጣሚ ተዋናይ እንዲሁም ጋዜጠኛ የሆነው አበባው መላኩ የመጽሃፍ ምርቃት ስነ ስርዓቱ በስኬት እንዲጠናቀቅ ወዲያ ወዲህ ይሯሯጣል….. ፡፡ የተወሰኑ ሴት ግጥም አቅራቢያን የክት ልብሳቸውን እየቀየሩ በሃበሻ የባህል ልብስ እየደመቁ ብቅ ብቅ ማለት ጀምረዋል……! ፡፡ ከመድረኩ በስተጀርባ የማሲንቆ ድምጽ ይሰማኛል ማን እንደሚጫወት ግን ለማወቅ አልቻልኩም ልስልስ ያለ የአንባሰል ቅኝት…..!፡፡ ሙዚቃ በጣም እወዳለሁ በተለይ ባህላዊ የሃገሬ ቅኝቶች የቤተሰብ ያህል እንቀራረባለን መታገስ አልቻልኩም ወደ መጸዳጃ ቤት የሚሄድ መስዬ ከመድረኩ በስተጀርባ የማሲንቆ ድምጽ ወደሚሰማባት አቀናሁ፡፡ለማመን በሚያዳግት ሁኔታ በህልሜም በውኔም አገኘዋለሁ ብዬ ያላሰብኩትን እጅግ በጣም የማደንቀውን፤የማሲንቆ፤የክራር፤የበገና ተጫዋች ድምጻዊ እና የሙዚቃ አስተማሪ የሆኑት አንጋፋው ሁለገብ አርቲስት አለማየሁ ፋንታ ናቸው………! ደስታዬን መቆጣጠር አቃተኝ ዘልዬ ተጠመጠምኩባቸው……!፡፡እ…ቅ……ፍ አድርጌ ሳምኳቸው፡፡ ለደቂቃዎች ትኩር ብዬ ተመለከትኳቸው….!፡፡ እኔን ተከትሎ የመጣው በዝግጅቱ ላይ የግጥም አቅራቢ የሆነው ወዳጄ በግርምት ትኩር ብሎ እየተመለከተኝ ነው……!፡፡ ጊዜ ሳላጠፋ የፎቶ ካሜራዬን አቀበልኩት እናም ምስላቸውን ከምስሌ ቀላቀልኩት ለኝህ አርቲስት ከዚህ በላይ ምን ማድረግ እችላለሁ? በጣም እንደምወዳቸው እንደማደንቃቸው ብዙ ጊዜ ላገኛቸው ሞክሬ እንዳቃተኝ ዛሬ በልዩ አጋጣሚ ስላገኘኋቸው በጣም ደስ እንዳለኝ ከእድሜዬ ላይ እድሜ ጨምሮ እንዲሰጣቸው ተመኘሁላቸው፡፡ ከወገባቸው ጎንበስ በማለት ምስጋናቸውን አቀረቡልኝ ፡፡ ትህትናቸው ልብ ይነካል….እድሜያቸው እየገፋ ነው፡፡ ሃገሬ ካፈራቻቸው አቻ ታዋቂ ታላላቅ አርቲስቶች በህይውት ከቀሩ  አንዱ ናቸው ዛሬም ግን ንቁ አዕምሮ ታድለዋል…..! በያሬድ ሙዚቃ ትምህትር ቤት የባህል ሙዚቃ መሳሪያዎችን በማስተማር በርካታ ሙዚቀኞችን በማፍራት ለቁም ነገር አድርሰዋል አሁን ግን በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማወቅ አልቻልኩም ሰፊ ጊዜ አግኝቼ ሙሉ ህይታቸውን በኪነጥበብ ዙርያ ስላካበቱት ልምድ ስላጋጠማቸው አስደሳችና አስቸጋሪ ጊዜያት ለትውልድ የሚተላለፍ ህያው ቃላቸውን ቀርጾና አቀናብሮ ለቀጣዩ ለትውልድ ማስተላለፍ ተመኘሁ ፡፡ነገር ግን ሌሎች በዚሁ ዙርያ ሃላፊነትና ተቆርቋሪነትን በማሳየት የምኞቴን ይሞላሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ከመሰናበታችን በፊት ግን ከሚከረክሩት ማሲንቆ ተከትዬ አንጎራጎርኩላቸው በጣም በመገረም ድምጼ እንደሚያምር ጊዜ ቢኖር በደንብ እንደምንጫወት ሙዚቃ ብጫወት እንደሚያዋጣኝ መሰከሩልኝ…… ውስጤ በደስታ ሙቀት ሲሞላ ተሰማኝ…….!፡፡ ከዚህ በላይ መቆየት አልቻልኩም የመጽሃፍ ምርቃቱ ሊጀመር ነው ተመልሼ ወደ አዳራሹ ገባሁ፡፡

የመድረክ መሪው ጥሪ የተደረገላቸውን የበዓሉን እድምተኞች በማመስገን የእለቱ የክብር እንግዳ ዶ/ር በድሉን በማስተዋወቅ የድግሱን መጀመር ሲያበስር ለዚህ የግጥም መጽሃፍ ምርቃት ለማድመቅ ጥሪ ሲቀርብላቸው ያለምንም ማመንታት በደስታ የተቀበሉትንና ወጣት ጸሃፍትን በማበረታታት የበኩላቸውን እየተወጡ የሚገኙትን ሙያቸውን እንዲሁም በሙዚቃ ሊያዝናኑን በመሃከላችን የሚገኙትን አርቲስት አለማየሁ ፋንታን ወደ መድረክ በመጋበዝ የድግሱ መክፈቻ መሆኑን አበሰረ፡፡ በዝምታ ተሞልቶ የነበረው ትንሿ አዳራሽ በእድምተኞች ጭብጨባና እልልታ ደመቀ…….! አርቲስቱ ወደ መድረክ ብቅ ሲሉ ሁላችንም ከመቀመጫችን በመነሳት በጭብጨባ ተቀበልናቸው ፡፡ አጸፋውን ከወገባው ጎንበስ በማለት መለሱ……!፡፡ ማሲንቆና ክራራቸውን ይዘዋል ፡፡ ግርማ ሞገሳቸው  ይበልጥ ገዝፎ ታየኝ……በሙሉ ስሜት ደስታና ሙላት በቀጥታ ስለ ሃገራችን አምስቱ የሙዚቃ ቅኝቶች ፤ስለባህላዊ ሙዚቃ መሳሪያዎች፤በተለይ ስለግርፍ ማሳሪያ ስለሆኑት ማሲንቆ፤ክራር እና በገና አንድነትና ልዩነት፤ አመጣጥና ታሪካቸው ልብ በሚመስጥ የአተራረክ ስልታቸው ማስተማር ጀመሩ……፡፡መርፌ ቢወርቅ በሚሰማ የአዳራሹ ጸጥታ ድባብ በስሜት ተሞልተን እያዳመጥናቸው ነው….! እውነት ለመናገር ከማውቃቸው በላይ ከግምቴ ልቀው አገኘኋቸው ፡፡ ሙያቸውን….. ባህላችንን…… ልምዳቸውን …..የሚያውቁትን ለማሳወቅ ያደረጉት ጥረትና ፍላጎት ይበልጥ እንዳከብራቸው አደረገኝ፡፡

                                                                               ©  ©  ©

              የዚህ ጽሁፍ ዓላማም በዋናነት ቀደም ሲል ለመጥቀስ እንደሞከርኩት በዋናንት “የዝምታ ጩኅት” የግጥም መድብል ይዘትና በመድብሉ ስለተካተቱት የግጥም ስራዎች አንስቶ ለመወያየት ቢሆንም ቅሉ በዚህ አይነት ፕሮግራም ላይ የሚጋበዙ በተለያየ የሙያ ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ታዋቂና ተጽእኖ ፈጣሪ ግለሰቦችን ጥሪያቸውን አክብረው የስራ እና የእረፍት ጊዜያቸውን ሰውተው ሙያና የልምድ ተሞክሮአቸውን ለእድምተኞች በሚያስተላልፉበት ጊዜ የሚገኝ እውቀትና በተሰማራንበት የሙያ ዘርፍ ዓይነት ትምህርት ቤት ቁጭ ብለን ከምናገኘው እውቀት በላይ ከፍተኛ ዋጋ ያለው መሆኑን ጠቁሞ ፤የሚገኘውን አጋጣሚ እንደማወቅ መረዳት መጠናችን እንድንጠቀምበትም ጭምር በማሰብ ነው……!፡፡

አርቲስት አለማየሁ ፋንታ መድረኩን ለአበባው ከመልቀቃቸው በፊት ማሲንቆና ክራር እየቀያየሩ ሙዚቃ ጋበዙን…..በአንቺ ሆሄ ቅኝት ሲጫወቱ የግጥም ስንኙ አሁን ድረስ ውስጤ ቀርቷል…….                      

ሀር የመሰለው አፍሪካ ጸጉርሽ

ሁሉን የሚጠቅሰው አሜሪካን አይንሽ

ዋሽንግተን ዲሲ በረዶ ጥርስሺ

የሚያረገርገው ብራዚል ሽንጥሺ

ተረከዝሽ ሎሚ ቶኪዬ ባትሽ
ደምግባትሽ ለንደን ፓሪስ ጠረንሽ
ዓለም መልከ መልካም በጣም ቆንጆ

እስቲ ፍቀጂልኝ ትንሸ ላጫውትሽ፡፡

                                  ©   ©   ©

               ሁለገቡ አርቲስት አበባው መላኩ መድረኩን ይዞታል….! በግራና በቀኝ የተጠመዱት ካሜራዎች የመድረክ መሪው ላይ አነጣጥረዋል….የእለቱን የፕሮግራም ዝርዝር በዝግጅቱ ላይ ስለሚቀርቡ የግጥም ስራዎችና አቅራቢዎች ቅደም ተከተል እንዲሁም በኪነጥበብ ዙርያ በእንደዚህ አይነት ዝግጅቶች ላይ ስላጋጠሙት ጣፋጭ ትዝታዎች ይጠቅማል ያለውን ሁሉ አንዴ ፈገግ አንዴ ኮስተር እያለ በሚያስገመግም ድምፁ ይሄ ፈረንጆቹ (golden voice) እንደሚሉት ልብ ሰርስሮ በሚገባ ሰምና ቅኔ ባዘለ አነጋገሩ መላውን እድምተመኛ ተቆጣጥሮታል…..! እንዴት መታደል ነው፡፡ የኔማ ይለያል ጆሮዬ አያን አይኔም ጆሮ ሆኖ በስስት እያዳመጥኩት ነው…..ከዚህ በፊት አይቼው ሰምቼው አላውም ……በኪነ ጥበብ ፤በስነ ጽሁፍ  መውደድና ፍቅር ህይወቴ ከአዲስ አበባ ርቄ መኖሬ ምን ያህል እንደጎደለብኝ ይበልጥ አሁን ነው የተሰማኝ……..አዎ በጣም ርቄያለሁ….. ከኔ በስተቀኝ በኩል የተቀመጠው ግጥም አቅራቢ ወዳጄ የሁኔታዬን ግር ማለት ተመልክቶ ትንሽ ስለ አበባው ሊያስረዳኝ ሞከረ፡፡


             አበባው መላኩ ጋዜጠኛ ነው…..ገጣሚ ነው፤“ ከራዲዮን ” የሚል የግጥም መድብል አለው የፊልም ቲያትር ተዋናኝ ነው፡፡ በቅርቡ አንድ የኤሌትሪክ ምሰሶ ላይ “ ቀለምና ህልም ”የሚል ማስታወቅያ ላይ ተለጥፎ አይቸዋለሁ፡፡ በእንደዚህ አይነት ዝግጅቶች ላይ ጥሪ ሲቀርብለት ያለውን የጠጣበበ ጊዜ መስዋት በማድረግ በሙሉ ፈቃደኝነት መድረኮችን ይመራል ፤ያስተባብራል ያለምንም ጥቅም ለኪነ ጥበብ የሚከፈለውን ሁሉ ይከፍላል…..!፡፡ ቀን እና ሰዓቱን አላስታውሰውም ይሄን ሰው የማወቅ ጉጉቴ ጨምሯል…….! ወደ ምኖርባት ናዝሬት ከተመለስኩ በኋላ አንድ ቀን የስራ ውሎዬን አጠናቅቄ ለሰራተኞች በተዘጋጅው የትራንስፖርት መኪና ላይ ተቀምጫሁ…..መሪውን የጨበጠው ሾፌር መኪናው ላይ የተገጠመውን የሬድዬ ጣቢያ እየጎረጎረ ነው እድገት የሆነ ኤፍ ኤም ጣቢያ ላይ ሲደርስ ፍለጋውን አቆመ፡፡ጣቢያው ጣራ ላይ ድንገት እንደፈሰሰ የበረዶ ናዳ እየተንሿሿ ነው፡፡ በዚህ ዓይነት መንጫጫት ውስጥ የአበባው መላኩን ድምጽ መለየት አያቅትም…..! ድንገት ከተቀመጥኩበት ዘልዬ የሬድዮ ድምጽ ማስተላለፊያ ስፒከር ላይ ጆሮዬን ተለጠፍኩ…..! ጋዜጠኛው ሁለት አማተር ሰዓሊያንን እያነጋገረ ነው…አጠቃላይ ስለ ስዕል ስራዎቻቸው ዛሬ ለቃለ መጠይቅ ስለተጋበዙበት  ጉዳይ እና በጉዳዬ ላይ የራሳቸውን አስተዋጽዖ ለማድረግ ምን እንዳነሳሳቸው በጥያቄና መልስ እየተጨዋወቱ ነው….. ፡፡ ሬድዮ ጣቢያው አይሰማም በግርድፉ ግን የነገሬን ጭብጥ ስለሚደግፍልኝ የሰማሁትን ላካፍላችሁ….፡፡ እነዚህ ሁለት ሰዓሊያን የአንድ በጎ አድራጎት ድርጅት የአቅም ግንባታ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ያዘጋጃል….. እናም እነዚህ አርቲሳቶች ከሁለት በላይ ስእሎቻቸውን ለዚሁ በጎ ምግባር የስዕል ስራውቻቸውን በማቅረብ ከስዕሉ የሚገኝውን የሽያጭ ገቢ ሙሉ ለሙሉ ለመስጠት ወስነዋል…፡፡ ጋዘጠኛው ጠየቀ “ ለመሆኑ የስዕሉ ጆሮ ላይ ስንት አንጠለጠላችሁበት? ” አላቸው “እንደኛው ይሄን ያህል አንደኛውም እንደዚ ” መለሱ

ጋዜጠኛው ተከተለ “ በጣም ደስ ይላል…..ታድያ እንዴት ነው ሽያጩ? ” መልሶ ጠየቃቸው

“ ይገርምሃል ስድስት ሺህ ብር የቆረጥንለት ስዕል ሰላሳ ሺህ ብር አወጣ በጣም ነው ደስ ያለን ” ፡፡ አሉትና የሚንጫጫውን የሬድዮ ሞገድ ሰንጥቆ የደስታ ሳቃቸው ተሰማኝ……!፡፡ ጋዜጠኛ አበባው መላኩም ቀጠለ  “ ለነገሩ እኔ አልደነቀኝም…… ገምቼ ነበር የሰው ልጅም እኮ ዋጋው የሚጨምረው በጎ ማድረግ ሲጀምር ነው ፡፡ ያደረጋችሁት ሁሉ በጣም ጥሩ ነው በርቱ ” አላቸው፡፡ አዎ ልክ ብሏል በጎ ማድረግ በብዙ መልኩ ይገለጻል……፡፡ ያለውን በመስጠት ፤ተሰሚነቱን በመጠቀም…….፤እውቀቱን በመለገስ…….ወዘተ…..፡፡ የዚህ የሚገኘው ትርፍ ዘመን ተሸጋሪ ከምንም በላይ የህሊና እርካታን የሚሰጥ ይመስለኛል፡፡ ይሄንን ነው አበባው ላይ ያየሁት ፡፡ እኔም ልጨምርለት…የሰው ልጅ በሚያሳልፈው የህይወት ዘመኑ….. ጉዞው……የስኬቱ ቁልፍ ፤በተሰማራበት የስራ ዘርፍ ሁሉ የተሰሚነቱ ሃይል መጨመር ትልቁን ስፍራ የሚወስደው የአስተዳደጉ ውጤት እና በዙርያው ባሉ የማህበረሰቡ ተጽዕኖ  ይመስለኛል፡፡ እናም እሩቅ ተጉዘን እማኝ መቁጠር ሳያስፈልግ አሁን የምናወራለት ሁለገቡ አርቲስት ላይ ለማየት ችያለሁ ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው……አንድ የመስሪያ ቤት ወዳጄ ጋር ስለ ዝምታ ጩኅት የምረቃ ዝግጅት ፤ በዝግጅቱ ላይ ስላጋጠሙኝ አስደሳች ገጠመኞች በፎቶግታፍ አስደግፌ እያጫወትኩት ነው…..፡፡ ድንገት እኔና አበባው ለማስታወሻነት ከተነሳነው ፎቶግራፍ ላይ አይኑ ተተክሎ ቀረ…….፡፡

“ አበባው መላኩን ከዚህ በፊት ታውቀዋለህ? ” አለኝ በመደነቅ

“ ኧረ አላውቀውም በዚህ ዝግጅት ላይ ነው የተዋወቅነው ” አልኩት፡፡ አንዳች ነገር ሊነግረኝ እንዳሰፈሰፈ ፊቱ ላይ ይነበባል ፡፡ “ ይገርምሃል…….” አለና አንገቱን ቀና በማድረግ በዓይኖቹ አድማስን ሰንጥቆ ለደቂቃዎች እሩቅ ተጓዘ……..፡፡ እኔም ታሪኩን ለማወቅ ጉጉቴ ቢጨምርም ከተሳፈረበት የትዝታ ፈረስ እስኪወርድ በትግስት ጠበኩት……..

ይገርምሃል አበባውን የማውቀው ሃረር ከተማ ነው አንድ ላይ አድገናል ሃረር ሰንበት ትምህርት ቤቶች  በሙሉ ሃለፊ ነበር ዲያቆን እንደነበረ ታውቃለህ? እጅግ የሚከበር የቤተክርስቲያን አገልጋይ ቤዛ መዘምራን እሱ የሚመራው የምስራቅ ሃረርጌ የሰንበት ት/ቤት ነበር ፤ የሚደመጥ፤ ከአንደበቱ የሚወጣው ቃላቶች ሁሉ ቅኔ ልውስ የሆኑ ብቻ ምን ልበልህ እጅግ ሙሉ ሰው ነበር……..! ፡፡ እንደውም በወቅቱ ማንም ሰው እናት አባቱ ባወጡለት ስም የሚጠራው አልነበረም (ወንድም ጋሼ) ነው የሚባለው፡፡ ዛሬ እዚህ ስኬት ላይ መድረሱ በጣም ነው ደስ ያለኝ ” አለና የትዝታውን ዳራ እዚህ ላይ ቋጨ……፡፡ እኔ ግን በሱ ፈረስ ተሳፍሬ በትዝታ ወደ “ ዝምታ ጩኅት ” ዝግጅት ተመለስኩ ፡፡

                                    ©     ©     ©

             በፕሮግራሙ መሰረት የግጥም መድብሏ በዶ/ር በድሉ በይፋ ከተመረቀች በኋላ እንደቅደም ተከተላችን በተጋበዙ የግጥም አቅራቢዎች የራሳቸውንና ከተመረቀችው መጽሃፍ ልባቸው የፈቀደውን ለተመልካቹ ማቅረብ ጀመሩ….፡፡ እኔም ተራዬ ደረሰና ስሜ ተጠራ…የሆነ አንዳች የፍርሃት ስሜት ውስጤን ሲወረው ይሰማኛል፡፡ አዎ እንደዚህ አይነት መድረኮች ከመሳትፍ ርቄ ነበር.. የሰው አይን እንዴት ያስፈራል….?! ፡፡አማራጭ የለም እራስን ማጀገን ነው ሙሉ ሃይሌን አሰባስቤ ከአትሮኖስ አጠገብ ቆምኩ…….፡፡ ምስጋና በማቅረብ የግጥም ስራዎችን ማቅረብ ጀምሬያለሁ….. ፡፡ አርቲስት አለማየሁ ፋንታ ከመድረኩ በስተጀርባ ሆነው ሳይሰለቹ ለሚቀርቡ ግጥሞች ሁሉ በማሲንቆ ጥኡም ዜማ በማጀብ እየተጫወቱ ልዩ ድባብ ፈጥረዋል …..እውነት ልብ ይመስጣል…. ከመድብሏ ውስጥ በዛች በተጣበበ ጊዜ ውስጥ አጣጥሞ አንብቦ መርጦ ማቅረብ ይከብዳል ፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ድንገት ከረጅም ዓመት በፊት የጻፍኳት ከኔ የግጥም ርእስ ጋር ተመሳሳይ ርዕስ ካላት ግጥም ጋር አይኔ አረፈ…፡፡ለግጥሞቹ የተሰጣቸው ርዕስ ተመሳሳይ ቢሆንም የያዙት ጭብጥ ፈጽሞ አይገናኝም ፡፡ እዚህ ጋር አንድ ነገር ተምሬያለሁ፡፡የሰው ልጅ የተለያየ ያሳለፈው ትዝታ የተለያየ የመናፈቅ ስሜት ይኖረዋል እብደየስሜቱ ግን የሚገልጽበት ቃልና መንገድ አተያይ ይለያያል፡፡ የኔን አይኔን ባይኔ ልተውና እስቲ ከመድብሏ ያነበብኳት ጀባ ልበል፡፡

አይኔን ባይኔ

አይኔ ከአይኔ ተገጣጥሞ አሻራ ማየት ስችል፤

እንባዬ እረጋግፎ ቆዳ ልብሴ ሲከሳስል፤

እግሬ ሲሄድ ወደ ጉድጓድ የእድሜዬ ክር ተጠምጥሞ፤

መኖር ፈለኩ እንደገና እኔን ባየው ስሬ ቆሞ ፡፡

                                                                          ©    ©    ©

          አዎ አንድ ሰው በህይወት ቆይታ ዘመኑ እንደተሰማራበት የስራ ዘርፍ በተለያየ ሁኔታ ባልጨረሰው ቤት ስራ ሲቆጭ…..በእድሜው አመሻሽ የነገን ብርሃን ሲመኝ የሚያሳይ እና በጊዜያችን እንድንጠቀም የሚነግረር መሰለቺኝ፡፡ እኔም ካልታተመው የግጥም መድብሌ ለእድምተኞች ያቀረብኩትን እነሆ….

እሳት ያልገባው ሃረግ

ህይወቴን በሸራ ወጥሬው በቀናት፤

ብሩሼን ጠልቄ ባልገባኝ ቀለማት፤

ስሞነጭር ገጼን ክፍ ክፋቱን ትቼ፤

በሰም ባልተቋጨ ቅኔውን ፈትቼ፤

……………….ሃቅ እውነቱን ግቼ፤

ተንጠልጥሎ ቀረ የሰቀልኩት ሸራ፤

ሳልፈልገው መሽቶ ሳልፈልገው በራ፡፡

                                                                      ©    ©    ©

                                                                          • • •

           የምጥ ያህል የግጥም ንባቡን ጨርሼ ተቀመጥኩ፡፡ አሁን ቀድሞ የነበርኩበትን ቦታ ቀይሬ ተቀምጫለሁ…፡፡ አርቲስት አበባው መላኩ ከተቀመጠበት የፊት ረድፍ ከጀርባው ነኝ…፡፡ ከመድረክ ላይ ስወርድ “ቆንጆ ነው በርታ” በሚል ማበረታቻ በዓይን፤አንገት ንቅናቄ  አሳየኝ…..፡፡ ወንበሬ ላይ ከተቀመትኩ በኋላ ወደ ጆሮው በጣም ተጠግቼ በጣም እንደማደንቀው እንደማከብረው ገለጽኩለት….አጸፋውን በምስጋና መለሰልኝ የግጥም መድብሉ የት እንደሚገኝ ጠኩት…… እሱም አሁን እንደማላገኘው ወደፊት ግን ድጋሜ ለማሳተም እንደሚቻል በአጭር ቃል መለሰልኝ……፡፡ ጊዜ የለውም ከዚህ በላይ ማውራት አላቻልኩም ሙሉ ልቡ ወደ መድረኩ ተንጠልጥሏል ገጣሚያን በየተራ የግጥም ስራዎቻቸውን እያቀረቡ ነው…….ተራው ደረሰና የቀድሞው ኢትኦ እንዲሁም የተለያዩ የግል ጋዜጦች ከተራ ጋዜጠኝነት አንስቶ እስከ ዋና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ወሰን ሰገድ ገብረኪዳን ቦታውን ተረከበ……..!፡፡ ምስጋናውን በማቅረብ ከመድረኩ ጀርባ በስተቀኝ በኩል በትልቁ ሸራ ላይ ተጽፎ የተለጠፈውን ጽሁፍ በማመላከት የኤጀንሲው አርማ እና ማስታወቅያ ጽሁፍ ላይ ቅሬታውን አቀረበ ፡፡ መጀመርያ አልገባኝም ነበር …..በኋላ ግን በጉልህ በሚታይ ነገር ግን ትኩረት ያልተሰጠው የሚመስል ጽሁፉ የፊደል ስህተት አለበት እንዲህ ይላል……(የኢትዮጲያ ብሄራዊ ቤተመዛግብትናቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ ) ይላል ጋዜጠኛው ቅር ያለውና በዛ ፍጥነት አይኑ ውስጥ ገብቶ ለማረም የሞከረው  (ጲ)የምትለዋ ፊደል ስህተት እንደሆነና(ጵ) ተብሎ መጻፍ እንዳለበት የኢትዮጵያ ተብሎ መታረም እንዳለበት በማስዘንዘብ ወደ ግጥም ስራው ገባ ……፡፡ ቀደም ሲል ለመግለጽ እንደሞከርኩት ከዚህ በፊት ከጋዜጠኛው ጋር ትውውቅ የለንም ስራዎቹንም አላውቃቸውም (ህዝብ ማለት) የምትለዋ ግጥሙ ግን ለመተዋወቃችን መሰረት ሆነች፡፡ እስቲ ግጥሟን አንብብን እንመለስ…..፡፡   

                  
ሕዝብ ማለት!?
ይኼ ሕዝብ ማለት
…. ወንዝ ነው ይፈሳል
ቦይ ከቀደዱለት መውረዱን ይወርዳል- መቅናቱን ይቀናል፤
ይኼ ሕዝብ ማለት…. የሰው ጥርቃሞ
ላቆመው የሚቆም ባዘመመው ዘ’ሞ
ልውጥ ነው መልከኛ ለአምናና ለከርሞ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ልክ እንደወንዝ ውሃ ድንጋይ ‘ሚያላጋ - ድንጋይ ‘ሚያናግር
በድልቂያ ጭብጨባ ልብን የሚያሳውር- መንፈስ የሚሰብር
ተዓምረኛ ነው- በአንድ ወግ ‘ማይረጋ
ባሻው አሸብሻቢ አመድ ሲሉት ሥጋ- ባልጋ ሲሄድ መንጋ፤
በግ ሲሉት እረኛ
ከሳሽ ሲሉት ዳኛ
ሁሉንም የሚሆን እንደሁሉ አዳሪ
መጣ ሲሉት ነጓጅ ሄደ ሲሉት ቀሪ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
እንደሁሉ አዳሪ
እንደሁሉ ኗሪ
ሁሉን ቻይ ፍጥረት ነው፣ ሁሉን ቻይ ኤልሻዳይ
የሚያይ መስሎ ‘ማያይ- ያላዩትን የሚያይ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ለክስ ‘ማይመች ለፍርድ ‘ማይቀና ፍጥረቱ ልዩ ነው
እዚህ ሲሉት እዚያ የሚገኝ መንትያ
ልክ እንደሸማኔ ጥበብ መወርወሪያ
ውስጠቱ ነው ልቡ- የእምነቱ ማደሪያ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ልክ እንደወንዝ ውሃ ወራጅ ነው አቆልቋይ
ከላይ አለ ሲሉት ከታች ወርዶ ‘ሚታይ
ወርዷል ሲሉት ከታች የሚነግሥ ወደላይ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
የምን ወንዝ ብቻ ባህርም ይሆናል
ሲያሻው ውቅያኖስ ማ‘በሉም ይንጣል፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ሳይታሰብ ሰግሮ ሳይታለም ደርሶ
አለ ሲሉት የለም ይሄዳል መልሶ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ሲወርድ ያዋርዳል- ከፍ ሲል ያስቀናል
እንደደራሽ ውሃ አሳስቆ መውሰድ- ማስመጥ ያውቅበታል፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ልክ እንደ ነቢይ ነው
በጊዜውም ቢሆን ባሻው ያለ ጊዜው፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
አንዳንዴ ግጥም ነው- አንዳንደዜ ቅኔ
አንዳንዴ ንስር ነው - አንዳንደዜ ዋ‘ኔ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት መመዘኛም የለው
መለኪያው ጊዜ ነው እርቦና መስፈሪያው
ሞላ ሲሉት ሥፍሩ የልኩ ጢምታ
የለም አይገኝም በሚዛን ገበታ፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
በበረደው በርዶ በሞቀበት ሞቆ
ሲመርም ጉፍንን ነው ልክ እንደመቅመቆ፤
ይኼ ሕዝብ ማለት ፍቺ የለው አቻ
እንዲሉ ነገር ነው ስልቻ ቀልቀሎ ቀልቀሎ ስልቻ
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ጡር ፈሪ ጦረኛ
ሲለው ሞገደኛ
ሳያሻው ምርኮኛ
የጊዜ ሥሪት ነው
ሲያደባም በጊዜ- ሲያሰላም በጊዜ- ሲሄድ ጊዜ አይቶ ነው፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
አንዳንዴ ሥምም ነው- አንዳንዴ መለያ
ሲያጠፋም ሲጠፋም የሌለው አምሳያ፡፡
በእርግጥ ሕዝብ ማለት ዝም ብሎ አይናቅም
በዝምታው ዘምቶ ሲያነሳም ሲጥልም
‘ሚያድን ‘ሚገልም፣ ቅንም ነው ቅን-ቅንም
የልቡ አይገኝም፡፡
ይኼ ሕዝብ ማለት….
ይኼ ሕዝብ ማለት…. ብታውቅ እወቅበት
ባታውቅ እወቅለት
አንዳንዴ ረሀብ ነው - አንዳንደዜ ቁንጣን
አንዳንዴ መልዓክ ነው - አንዳንደዜ ሰይጣን
እውነት እውነት እውነት ይኼ ሕዝብ ማለት….
አንዳንዴ ውሸት ነው - አንዳንደዜ እውነት፡፡

                                                                              • • •

የግጥም ምሽቱ ደስ በሚል ሁኔታ ተጠናቀቀ የማስታወሻ ፎቶም ተነሳን……..ብዙ ነገር

 ተማርኩበት

5 comments:

  1. I appreciate you for taking time, struggling and trying to find your way inside the story you need to tell. I appreciate you for the deep breath you have to take before you share your feelings and exploration of the event. I see the big potential you have inside to share and shine more for the world…and besides you are appreciative of your peers and goodhearted man! Thank you for accepting my friendship request on facebook and God bless you!! Bisrat Alemu

    ReplyDelete
  2. አደም ወንድሜ፤ ትልቅ ሥራ ነው እየሠራህ ያለኸው፤ ድንቅ ነው፡፡ ድረ-ገጽህን ውድጄዋለሁ፡፡ ግፋበት - - - -

    ReplyDelete
  3. Adem yibel yemiyasegn new realy

    ReplyDelete
  4. gitim enditsif aberetatugn..............

    ReplyDelete
  5. የመድኃኒት ንግድ ሥራዬን ለማስፋፋት በተጠቀምኩበት ብድር ለመርዳት ሚስተር ቤንጃን ከሚያስፈልጓቸው በላይ አልፈዋል ፡፡
    እነሱ ለመስራት ወዳጃዊ ፣ ባለሙያ እና ፍጹም ዕንቁዎች ነበሩ ፡፡ እኔ ለማነጋገር ብድር የሚፈልግን ማንኛውንም ሰው እመክራለሁ ፡፡ Lfdsloans@outlook.com.WhatsApp ... +19893943740.

    ReplyDelete