Tuesday, June 5, 2012

ያልተላከው ደብዳቤ


            ያልተላከው ደብዳቤ
እስቲ ወደኋላ በትዝታ ልመልሳችሁ………..መቼም በወጣትነት በተማሪነት ወቅት እንደየ ጊዜና ዘመኑ የማይረሳ ጣፋጭና አስገራሚ የህይወት ገጠመኝ እንደምናሳልፍ እገምታለሁ ወይም ብጠረጥ የሚደንቅ አይመስለኝም፡፡
የኔን  የተማሪነት ዘመን እናውጋ……አንድ ገርል ፍሬንድ እንዲኖርህ ትፈልጋለህ እንበል ቀትታ ሄዶ ማነጋገር ነውር ነው ወይም ደግሞ የሚደፍርም የለም እሷስ ብትሆን ስታናግርህ አይደል……….! እናም እንዴት እንደምታናግራት ሊጨንቅህ ይችላል እናም በወቅቱ በሰፊው የተለመደው ደብዳቤ መጻፍ ነው የፍቅር ደብዳቤ እሱንም ቢሆን አዋቂ፤ምርጥ ጸሀፊ መሆን ይጠይቃል፡፡ማንም ተነስቶ ደብዳቤ አይጽፍም……የወደድካት ልጅ ልቧ እንዲራራ፤ያንተ እንደስትሆን ከፈለክ መጠንቀቅ ያስፈልጋል ቃላት መምረጥ አለብህ፤ጥቅስ መደርደር፤አባባሎችን መጠቀም ፤አበባ መሳል ፤ልብ ቅርጽ ላይ ጦር ሰክተህ ደም ማንጠባጠብ አለብህ ቢቻል ከደብዳቤው ጋር ደስ የሚል የህንድ ፖስት ካርድ ይሄ ሀሚት አፕ አቻ ከቆንጆ ሚስቱ ጋር ያለበትን ከጀርባው ከ ኤስ  ለ ቲ ብለህ ጽፈህ…… ፡፡ በቃ ምን አለፋህ ጥንቃቄ የተሞላበት ጽሁፍ ካልሆነ የልጅቷን ልብ አራራለሁ ብለህ ጭራሽ ልቧን አምርረኅው ቁጭ ትላለህ፡፡
አንድ የትምህር ቤት ጓደኛ ነበረኝ የፍቅር ደብዳቤ በመጻፍ የሚታወቅ እሱ የጻፈው ደብዳቤ የደረሳት ተፈቃሪ ልቧ የማይራራ የለም እውነት ይገርመኛል ሀሪፍ ጸሃፊ ነው በቃ ፍቅር  ሲይዝህ እሱ ጋር መሄድ ነው፡፡ ከዛ ልክ ሀኪም ዘንድ ወይም አጥፍተህ ዳኛ ዘንድ  እንደቀረበ ጥፋተኛ ትናዘዛለህ ውይም ችግርህን ታወያየዋለህ፡፡
#ምኗን ነው የወደድካት?; ይልሃል ፡፡ በቃ ትንሽ ማፈርህ አይቀርም ትሽኮረመማለህ….ግን ፍቅረኛህን ከማጣት አይበልጥምና ትናገራለህ፡፡ ይገርመኝ የነበረው ይሄ ጓደኛዩ ሲጠይቅህ ኮስተር ብሎ ነው በስሜት ተውጦ ያዳምጥሃል፡፡ አንተም ትናዘዛለህ…………
#እሷን እያየሁ እያሰብኩ ምግብ አልበላ ውሃ አልጠጣ አለኝ አማርኛ ትምህርት አረብኛ ሆነብኝ፤ እሷን ሳይ መራመድ አቃተኝ ትንሽ ጠጠር እንቅፋት እየመታኝ ይህው እግሬ ተላላጠ  
ወዘተ…..; ትነግረዋለህ እሱም አዳምጦህ ሲጨርስ የራሱን ጥበብ መጠበብ ይጀምራል፡፡
(እናንተስ የፍቅር ደብዳቤ ጽፋቹ አታውቁም?)……..                 
                           ! ! !
ደረጀ ፍቅሩ የሚባል ወዳጅ አለኝ መቼም ታውቁታላችሁ (ስርየት) የሚባል ፊልም ደራሲ ነው (ጋጋ) የሚባል አስፈሪ ገጸ ባህሪ የሚተውንበት
#አዲስ አበባ ደበረኝ;
 ሲለኝ ና እለውና ይመጣል ያለሁበት ሀገር እንገባበዛለን ቀዝቀዝ ያለ ቢራ እየጠጣን እንጨዋወታለን የማይነሳ የማይጣል ነገር የለም ሲበዛ ቀልደኛ ነው ጨዋታ ያውቃል የደረስኩትን የተወንኩበትን ፊልሜን እይልኝ አለና ጋበዘኝ በደስታ አየሁት፡፡ በቃ ከዛን ጊዜ በኋላ የአማርኛ ፊልም አይቼ አላውቅም የራሴ ምክንያት አለኝ በቀደም ግን እንዲሁ ከአንድ ወዳጄ ጋር በዚሁ ጉዳይ ስንነጋገር……. (ውይይታችን ይቆይ………. የፍቅር ደብዳቤ በሃገራችን ፊልሞች ግን ልጋብዛችሁ)

Wednesday, May 30, 2012

የምን ምናምንቴ !!!!










እንዲህ ነው !
ስነ-ግጥም…የውበት ልቀት ነው
ስነ-ግጥም…….የሰው ልጅ አእምሮ ረቂቅ ውጤት ነው
ስነ-ግጥም …….የራሱ ፍጻሜ አላማ አለው
ስነ-ግጥም……….የስነ ጽሁፍ ፈርጥ ነው፡፡
               © © ©

         ለዚህ ነው በስነ-ግጥም የሰው ልጅ ስሜቱን የሚጭረው ነገር ሲያገኝ የሚያለቅስበት፤የሚስቅበት፤የሚከፋበት፤የሚዝነናበት፤ወዘተ………፡፡   እናም እንደቀልድ ከላይ የገጠምኳትን ግጥሜን ለረጅም ጊዜ ሳጥኔ ውስጥ ቆልፌ በቅርቡ ትንሳዬዋን አግኝታ ለአቅመ ንባብ ስትበቃ በርካታ ገጣሚያን ልብ ውስጥ ገብታ በራሳቸው እይታ የተሰማቸውን ለማለት የበቁት……….፡፡ መቼም ምን ያህል ልቤን አንደነካኝ ቃላት አይፈታውም ! ሁሉንም አመሰግናለሁ ፊት አውራሪ ገጣሚ ዮሃንስ ሞላ ትልቁን ቦታ ይይዛል ከዚህ በኋላም መሰል ግጥሞች ይቀጥላሉ…………እኛም እንጽፋለን !!!! ፡፡
                    © © ©
       ቦንቡን
ቦንቡን  ካልፈራኸው  ንቀል  ከእንብርቷ
ይቆም  ከመሰለህ  ውበት  መለከቷ
በሸንቃጣ  ወገብ  እንዲህ  ተሞናድላ
በእንጆሪ  ከንፈር  በረዶውን  ስላ
ደረቷ  ሚሳኤል  መያዙን  ሳታውቀው
በአይኗ  ወላፈን  ፍቅርህን  ሳትፈጀው
መሞትን  ከመረጥክ
ትግደልህ  ብያለሁ  እሷም  እንድትገልህ  አንተም  እንደመረጥክ …….

,
አርአያ መርቲ መተሃራ
አቤት ስልጣኔ
የጆሮ ተወዶ  ዘንድሮ  ጉድ ፈላ
ምንስ  የቀረ  አለ  ያልተባሳ  ገላ
ውበት ነው፣እብደት  ነው  ወይስ  ስልጣኔ
ይህው  ጉድ  አሳየኝ ዝቅ  ብሎ  አይኔ
እምብርት  ወግ  ደርሶት  ጉትቻ  አጠለቀ
ተገንጦ  በይፋ  ይህው  ፀሀይ  ሞቀ
ቦዲ  የተባለው  መላ  ቅጡ  የጠፋ
ጡቶቿን  አጋልጦ  ያሳያል  በይፋ
ሚኒ  ደሞ ተብሎ  ጣል  የተደረገው
ሀፍረተ  ስጋዋ ይህው  አጋለጠው።
"
እብደት  ነው  ውበት ነው  ወይስ  ስልጣኔ"  ብዬ ቋጥሬ  ካስቀመጥኳት  ግጥሜ ከማስታወሻዬ  ላይ  የተወሰደች  ነች።

Tuesday, May 29, 2012

የበረሃዋ ገነት


ሽቦ ጊቢ
  ጊዜው እንዴት ይሮጣል……..ገምት ብትሉኝ አንድ ሀያ አመት አካባቢ ይሆነዋል፡፡ የአንድ ሰፈር የአንድ አካባቢ ልጆች ነን ደስ የሚል ጣፋጭ ጊዜ አሳልፈናል….የማይረሳ፤ፍቅር የተሞላበት ተናፋቂ ጊዜ…….. አሁን የሆነ ያህል እንደ አዲስ ይሰማኛል፡፡ በዘር ፤በቀለም ፤በሃይማኖት ፤በጎሳ በጥቅም ያልተከፋፈለ ንጹህ ፍቅር ያለበት…….፡፡ እንግዲህ ፌስ ቡክ (ፈቅጄ በገባሁ) ብየዋለሁ አንዱ አብሮ አደጌ የፎቶ አልበም ውስጥ አገኘሁት…… እጅግ ልቤ ተነካ በትዝታ እሩቅ ተጓኩ……በቀላሉ ተፈጥሮን ለማድነቅ የተለያየ ቦታ እንሄዳለን፤እንዝናናለን፤እንስቃለን፤እንደንሳለን፤እንጨፍራለን፤ ክፋት የለም ፤ምቀኝነት አይታሰብም፤ደግነት ግን በትልቅ ዙፋን ላይ ተደላድሎ የነገሰበት ወርቅ ጊዜ……..(ይሄ በሁሉም በወቅቱ የነበረ የሃገሬን ወጣትነት የህይወት ዘመን ይወክላል)፡፡ ዛሬ ሁሉም ተበታትኗል ፎቶውን ሲያዩ ምን ይሰማቸው ይሆን ?????፡፡
ስማቸውን ለማስታወስ ልሞክር (ቢንያም አለሙ፤ፍሬ ወይኒ፤ራሄል ተከስተ፤ትዕግስት(ሚጢጢ)ንጉሴ፤ተዎድሮስ ካሳሁን፤መስከረም ተከስተ፤ያሬድ ካሳሁን፤አማን ረዘነ፤ቆንጂት ሁሴን፤ዮሃንስ አሸብር፤ሰለሞን ተከስተ፤ስንታየሁ ካሳሁን፤ኢሳያስ ዮሴፍ፤አደም ሁሴን፤አራዶም ሰለሞን፤ሮቤል ረዘነ፤ዽጥሮስ ዳዊት፤ኤዴማ ሂዲ፤ቴዎድሮስ በየነ) እነሆ በረከት ብለናል፡፡  

                         የበረሃዋ ገነት
ከወደ ምስራቅ ጸሀይ መውጫ
ያ'ድማስ ጮራ ህብር መገለጫ
ያላፊ አግዳሚው ፍኖት መሳለጫ
የከረዩ ውበት ያ..ክምክም ጎፈሬ
የኢቱ የአፋር ካፎት የሻጠው ጊሌ
የብሄር ስብጥር የግራር ዛፍ ፍሬ
ከበረሃ መሀል ያለሽው መንደሬ
የ'ትብቴ ማረፍያ እልፍ ዓለም ክትሬ
ከፈንታሌ ጋራ ካዋሽ ወድያ ማዶ
ህብረት እንደ ማገር በፍቅርሽ ተገምዶ
የእህል ውሀ ነገር ካድማስ ወድያ ማዶ
ልቤን ካንቺው ትቼ አካሌ ተሰዶ
ፈገግታ§ን ውÂ ደስታው ከኔ ርቆ
ድንገት ከሳሎኔ ከመስታወት ቆሜ
ጥርሴ ላይ የቀረ ያኖርሺው ማተቤ
ተገልጦ የማያልቅ የህይወት አልበሜ
የማንነት ድርሳን መለያ ቀለሜ
ተዳፍኖ ያለውን የልጅነት ህልሜን
ከፍቼው ልተርክ የትዝታን ኪዳን
ጨልፌው ለመጋት ጥሜን ለአመሌ
ብእር ጦሬን ሰበኩ ዝምታን ሰብሬ፡፡
                                           ከስንኝ ቋጥሬ ቃላት ብዘራልሽ
አደባባይ መሐል ማ‘ሌት ብቆምልሽ
አልሆንልህ አለኝ ጣፋጭ እንደምርትሽ፡፡

Thursday, May 24, 2012

ልምሰል የሞላለት


ልምሰል የሞላለት
አዎ "ልምሰል የሞላለት ! "
በልቸ ጠጥቸ ስለኖርኩ በድሎት i
መብቴ ተገፎ አጥቼ ነጻነት
በስደት ሃበሳ ስኖር ስንከራተት፤
የደላኝ ይመስላል ! አኗኗሬን ሲቃኙት፤
የደላኝ ይመስላል ! ተክለ ቁመናየን መላብሴን ሲያዩት፤
የደላኝ ይመስላል! ስናገር ሲያደምጡኝ የምኖር በስኬት !
ታዲያሳ. . . !
በአደባባይ ልሳቅ ከቶ ምን አለበት
በደስታ ልምነሽነሽ ልምሰል የሞላለት
ኑሮ ግብግቡን አስተውለው ሲያዩት፤
ድብብቆሽ ኑሮ፤ አለፋውን ስቅየት
የመንገዱን ርቀት የሰው ልጅን ክፋት፤
ሲታዘቡት ውለው ሲያሰላስሉ ቢያድሩት፤
ምስለኔያችን ከፍቶ ሲደሰኩት ኩሸት፤
ሰብዕና ጠፍቶ ሰው ሁሉ ሲራኮት፤
ወገኔ ዝም ብሏል ቤቱ እስኪደርስበት፤
ደፋር ይናገራል እሱ ምናለበት
"
እድል እጣቸው ነው የተፈጠሩበት"
"
ለምን መጡ" ይላል መድገፉ ጠፍቶት፤
ይለናል ጎረምሳው መደገፉ ጠፍቶት
ድምጽ ማሰማቱ ፤ውሃ ማቅረብ ገዶት
እናም. . .
ስላየሁ በአይኖቸ ይህን መሳይ ትንግርት፤
ስላየሁ ህይዎቱን የዳፋ ቀማሹ የመሪሩን ስደት፤
ያስታግሰው እንደሁ የንዳድ ቃጠሎ የብሽቀቴን ብርታት፤
ድብቅ ሽሽግ ብየ . . .ሲለኝ አለቅሳለሁ ለመረረው ህይዎት፤
አዎእውነት ብለሃል ወንድም አደም
ይህ ነው የእውነቱ ገጽታ የዚህች አለም . . .
"
በጨለውማ ተስፋ ፤ጥርሴ ጧፍ ከሆነ
የህይዎቴን ግርዶሽ ገላልጦት ካደረ፤
ምናለ ልሳቀው ባንች ሆየ ቅኝት
ልንከትከት በዜማ ልምሰል የሞላለት !"
                     ©  ©  ©
        ወዳጀ አደም ሁሴን ዘራፍ አስባልከኝ እኮ ) ! ግጥም ደስ ይላል . . . የላክልኝ ግጥም ውስጤን ነካችውና ከተጋደምኩበት ይህችኑ ቋጠርኩልህ ! ስንኝ መገጣጠሙን በትክክል አሳክቸዋለሁ ባልልም ስሜቴን ካስረዳልኝ ይበቃል! ገጣሚ አይደለሁ እንዳንተ ! ለሁሉም ይህችም ላንተ ትሆን ዘንድ ፈቅጃለሁ !
ነቢዩ ሲራክ